Quantcast
Channel: Bawza
Viewing all articles
Browse latest Browse all 1835

ስለ ፍቅር! !!!!

$
0
0
 ስለ ፍቅር! !!!!

ፍቅር ሰውኛ ነው ። ዘሩም ሃይማኖቱም ሰው መሆን ብቻ ነው ። የሰው ልጅ ስለ ሰው መሆን ብሎ ሰውኛ የመዋደድና የመተሳሰብ እሴቶችን ያስቀድማል ። ለሰው ለማዘን ወይንም ለሰው ለማሰብና ከሰው ጋር በሰውነት ደረጃ ለመኖር ሃይማኖተኛ መሆን ቅድመ መስፈርት አይሆንም ። እንደ ሰው ለመኖር ሰው መሆን በቂ ነው ። የሰው ልጅ ሰው በመሆኑ ብቻ የሚጋራቸው ግዙፍ እሴቶች ሞልተውታል ። ሃይማኖት አብሮ ለመኖር ብቸኛውና ምትክ የለሽ ዋስትና ቢሆንማ ኖሮ ከግማሽ ህዝባቸው በላይ ኢ አማኒ ((ሃይማኖት የለሽ) ) የሆነባቸው የእስካንዲቪኒያ ሃገራት በእድገትና በሰላማዊነት ብሎም በደግነት ረድፍ ባልተገኙ ነበር ።

ያደግኩበት ማህበረሰብ የዘር የሃይማኖት ልዮነቶች ቢኖሩትም እንደ ሰው የሚጋራቸውን ስሜቶችና ፍላጎቶች አጉልቶና አስፋፍቶ መኖር ይችልበታል ። በልጅነቴ ሰውን ከመውደዴ የተነሳ ስለ ባልንጀሮቼ ፍቅር ስል እኔን የማይጎዳ እነርሱን ግን የሚያስደስት ነገር ፈጽሜያለሁ ። ያደግኩበት ሰፈር የሙስሊሞች ሰፈር በመሆኑ በረመዳን ጾም ጊዜ ባልንጀሮቼ ሲጾሙ ከነርሱ ፊት መብላት የነሱን ረሃብ መቀስቀስ እንዳይሆንብኝ በሚል ንጹህ የልጅነት እሳቤ ተነስቼ በጾም ወራት ከፊታቸው ላለመመገብ ጥረት አደርግ ነበር ። የልብ ጓደኝነቴን ለማሳየት ረመዳንን አብሬያቸው እጾም ነበር ። አብሮነቴንና ጓደኝነቴ የሚያስከፍለው ዋጋ ካለ የመስዋእትነት ፈቃጀኛነቴን ለማሳየት የባልንጀራነት ቁርጠኛነቴን ለማሳየት በትንሹ ስጾም እውላለሁ ። የመውሊድ ቀን ሁላችንም የወልዲያ ክርስቲያን ልጆች ከሙስሊም ወንድሞቻችን ጋር ዳንዮል አወል መስጂድ በሚደረገው የጸሎት ስርአት ላይ ዳና ዛውያው ስር እንገኛለን ። ባልንጀሮቻችን ሲደሰቱ አይተን እኛም ደስ ይለን ነበር ። ይህንን ቅን ድርጊታችንን ከሃይማኖት አንጻር ማየቱን ተውትና ቢያንስ ቢያንስ ትላልቅ ሸኪዎች በአባትነት ሲመርቁን አሚን እንላለን ። መልካም ምኞት ከጤናማ ማህበረሰብ የሚመነጭ ነውና ሰውኛ ዋጋችንን ይጨምራል ። የመረቀኝን ሽማግሌ የምርቃን ንያው እንጅ ሃይማኖቱ አያሳስበኝም ነበር ። ሃይማኖታችን ቢለያይም ሰው የመሆናችንን የጋራ ጸጋ የሚያጎሉ ስርአቶች የግድ ከሃይማኖት ጋር ብቻ የሙጭኝ ብሎ ማላዘን ከሰውኛ ሚዛን ማጉደሉን ደጋጎቹ አባቶቻችን አስተምረውናል ።

እንደነገርኳችሁ በየጁ ዳና ምድር በሚደረገው ስርአት ላይ ጓደኞቻችንን አጅበን መሄድ የባልንጀራነት ሃቂቃን እንደመወጣት እንቆጥረው ነበር ። ያኔ በልጅነቴ የመውሊድ ቀን በዳና ምድር ሲከበር እንደስከዛሬው ሳይሆን ጉዞው በእግር ስለሆነ ሙስሊም ወንድሞቻችን ብቻቸውን እንዳይሆኑ ጉዞና ዚያራቸውን ለማሳለጥ አብረን እንተም ነበር ። ጓደኞቻችን ጋር አብረን ስንጓዝ የሚመለከቱ ሙስሊም አባቶቻችን ከጓደኝነት በረካ አይለያችሁ! !! እያሉ ሲመርቁን አጥንታችን ይለመልም ነበር ። ይህንን ያደረግነው ለእምነቱ አምልኮ አልነበረም ። ይህንን አጋጣሚ ተጠቅመን ጓደኝነታችን ላይ የአብሮነት እሴት ለመጨመር እንጅ ። የመስቀል ቀንም ቢሆን ሙስሊም ጓደኞቻችን ለአምልኮ ሳይሆን የእኛን ደስታ ለማየት አብረውን ይሆናሉ ። አብሮነትና ጓደኝነትን ከአምልኮ ነጥለው የሚያስቡ ስለመሆናቸው ምድሩም ሰማዩም ይመስክር ። በየጁ ምድር ዛሬም ድረስ ይህ ደማቅ እውነት ህያው ሆኖ በዳንዮች ምድር ላይ ቀጥሏል ። አሁንም ዳና ምድሩ ይመስክር ። ታዲያ ይህንን ያደረግነው ተገደን ነው እንዴ? ?? ይህንን የኖርነው ሙስሊሞች አስገድደውን ነው እንዴ? ?? ኧረ ጎበዝ የቀመስነውንና የዳሰስነውን እውነት አየር ላይ በተንጠለጠለ ምኞት ልታስጥሉን አትሞክሩ ። እኛ በደጃችን የቀመስነውን ወጥ ጣእሙን ልትነግሩን ስትሞክሩ ትንሽ ይክበዳችሁ እንጅ! !!!

Mengistu Zegeye Facebook page

The post ስለ ፍቅር! !!!! appeared first on Bawza NewsPaper.


Viewing all articles
Browse latest Browse all 1835

Trending Articles